ክፍል ሁለት
"በአዲስ ኪዳን አልተጠቀሰም” የማለት አግባብነት
ሌላው የሚነሳው ሀሳብ በአዲስ ኪዳን ቅዱሳን እንደሚያማልዱ አልተጻፈም የሚል ነው፡፡ በመሰረቱ መጽሐፍ ቅዱስ
ተብሎ የሚጠራው ብሉይ ኪዳን እና አዲስ ኪዳን በአንድነት ነው እንጂ ለየብቻ በመነጣጠል አይደለም፡፡
ብሉይ ኪዳንን ብቻ ነጥሎ መቀበሉ ከአዲስ ኪዳን ተስፋ እንደሚለይና ስለ አዲስ ኪዳን የተናገረውን
ራሱን ብሉይ ኪዳንንም ሐሰተኛ ማድረግ እንደሆነ ሁሉ አዲስ ኪዳንን ብቻ ነጥሎ መቀበልም አዲስ ኪዳንን መሰረት የሌለው፣ ለመታመን
የሚያስቸግር፣ በመሀል የተከሰተ ተንሳፋፊ ያደርገዋል፡፡
አዲስ ኪዳንን የማያመለክት፣ የማይናገር ብሉይ ኪዳን እንደሌለን ሁሉ ብሉይ ኪዳንን መነሻ የማያደርግ
ለምስክርነት የማይጠራ፣ እውቅና የማይሰጥ አዲስ ኪዳንም የለንም፡፡ ያለን በአንድ መሰረት የታነጸ ብሉይ ኪዳንን እና አዲስ ኪዳንን
ያዋሐደ አንድ መጽሐፍ ቅዱስ ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን ተጠቅሶ ከሆነ በአዲስ ኪዳን አለመጠቀሱ አለመኖሩን እንዴት ሊያረጋግጥ ይችላል?
አዲስ ኪዳንና ብሉይ ኪዳን የሚገነዛዘቡ እንጂ ለየብቻቸው የቆሙ አይደሉም፡፡
ጌታችን በወንጌል ሕግን እና ነቢያትን
ለመሻር የመጣሁ አይምሰላችሁ ልፈጽም እንጂ ለመሻር አልመጣሁም፣ እነርሱም ስለ እኔ የሚመሰክሩ ናቸው፣ ሙሴንስ ብታምኑት እኔን ባመናችሁ
ነበር እርሱ ስለ እኔ ጽፎአልና…እያለ ብሉይ ኪዳንን ይጠቅሳቸዋል
እንጂ ለምስክርነት የማይበቁ፣ ቃላቸው የማይጠቅም አድርጎ አልጠቀሳቸውም፡፡
ይልቁን አታመንዝር ያለውን
ወደ ሴት ያየ የተመኘም፣ በውሸት አትማል ያለውን ከቶ አትማሉ…በማለት
በብሉይ ኪዳን የታዘዙትን አጽንቶአቸዋል፡፡ ከዚህ ሌላ በብሉይ ኪዳን ምሳሌ ሆኖ ሲሰራበት የነበረውን መስዋእት በራሱ እውነተኛ መስዋእትነት
ተክቶታል፡፡ ይህ ሁሉ ከፍታ እንጂ ዝቅታ፣ መስጠት እንጂ መንጠቅ አይደለም፡፡
በብሉይ ኪዳን ቅዱሳን ያማልዱ ከነበረ "በአዲስ ኪዳን ምንም አልተጠቀሰምና አያማልዱም"
የሚያስብል የአመክንዮ ሙግት መሰረት የለሽ ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን ስለ ሥጋዊ ጉዳዮች ያማልዱ ከነበረ በአዲስ ኪዳን ከሥጋዊ ጉዳዮች
በተጨማሪ ከፍ ባሉ፣ ስለ መንፈሳዊ ጉዳዮች ያማልዳሉ እንጂ አሁን ጸጋው ሲበዛ ጭራሹንም በዘመነ ኩነኔ የነበራቸው ጸጋ ይወሰዳል
ማለት ትርጉም አይኖረውም፡፡ ጸጋውን ሽተው የታገሉትን በጸጋ ላይ ጸጋ እየጨመረ ከፍ ያደርጋቸዋል እንጂ ዝቅ አያደርጋቸውም፣ ጸጋን
ይሰጣቸዋል እንጂ አይነጥቃቸውም፡፡
ስለዚህም በብሉይ ኪዳን ያሉ የአማላጅነት ጥቅሶችን በአዲስ ኪዳን ተጠቅሰዋልን ብለን ገና ምስክርነት የምንፈልግባቸው ሳይሆን ከአዲስ ኪዳን ዓላማ አንጻር በተጋድሎአቸው
ዐይነትና ብዛት፣ በሚሰጣቸው ጸጋ እና የማማለድ ስልጣን አድማስ ሰፍተው እና በዝተው የሚታዩ መሆናቸውን የምንረዳበት ነው፡፡
ሁለት
በአጸደ ነፍስ ቅዱሳን ያማልዳሉ ማለት የእግዚአብሔር ባሕርያት መገለጫዎችን ለሰዎች መስጠት
ነው ስለ ማለታቸው
አንዳንዶቹ ደግሞ በሚገርም ሁኔታ ቅዱሳን በአጸደ ነፍስ ያማልዳሉ ማለት ለእግዚአብሔር የባሕርይ መገለጫ
የሆኑትን ሁሉን አዋቂነትን፣ የአጸደ ነፍስ አማላጅነት በሁሉም ቦታ መገኘትን ስለሚጠይቅ እነዚህን ገንዘብ አድርገዋል ማለት ነው፡፡
ይህ ደግሞ ቅዱሳንን አማልክት ወደ ማለት ክህደት ይወስዳል ይላሉ፡፡
እነ ማን እንደሚጸልዩ ማወቅ በሃይማኖትና በምግባር ራስን ጠብቆ የአማላጅነትን ጸጋ ከመቀበል
የሚበልጥ ነውን? ነቢዩ ኤልሳዕ በአሁኑ ካለው ከቴሌቪዥን ቴክኖሎጂ ሊወዳደር በማይቻል ሁኔታ ስለ ሶሪያ ንጉስ የጥፋት ምክክር ጥርት
ያለን መረጃ ለይሁዳ ንጉስ ማድረሱ በዚያ በዘመነ ኩነኔ የተቻለ ከሆነ በዚህ በዘመነ ምሕረት ለዚያውም ነፍስ ነጻነቷን አግኝታ ከሥጋ
በላይ በምትሆንበት (በአጸደ ነፍስ) በኋላም ሥጋም ከነፍስ ጋር በምትስማማበት በሰማያዊ ቤት ለኤልሳዕ ከተሰጠው እውቀት የበለጠ
የማወቅ ጸጋ ለቅዱሳን(ቅዱሳን የተባሉት ሲጀመር ጸጋው የበዛላቸውን ነውና ፣ቅዱሳን ከሆኑ ጸጋው አላቸው ማለት ሌላን ምርምር የማይሻ ስሙ ላይ ያለ ቀጥተኛ ፍቺ ነው)
አይሰጣቸውም ማለት ከመጽሐፍ ቅዱስ ዐላማ በተለይ እንደ ተከራካሪዎቹ የክርክር መነሻ ከአዲስ ኪዳን አስተምህሮም ሆነ መገለጥ የሚጻረር
ዐለም ዘራሽ ስሁት አመክንዮ ነው፡፡
በሁሉም ቦታ መገኘት ለእግዚአብሔር ብቻ የሚሆነው በአካል በሁሉም ቦታ መገኘት በሚለው አስተምህሮ
ነው፡፡ የቅዱሳን ግን በአካል በሁሉም ቦታ መገኘት ሳይሆን በረድኤት፣ በመንፈስ በሁሉም ቦታ መገኘት ነው፡፡ ይህ ደግሞ የእግዚአብሔርን
የባሕርይ መገለጫ ለሰዎች መስጠት ሊሆን አይችልም፡፡ ታድያ ቅዱስ ጳውሎስ ገና በምድር እያለ በአካል ከእነርሱ በመለየቱ እኔ ምንም እንኳ በሥጋ ከእናንተ
ጋር ባልሆን በመንፈስ ከእናንተ ጋር ነኝ ማለቱ ትርጉም ላይኖረው ነውን፡፡
አንድ ምድራዊ ንጉሥ ምን በአካል ባይገኝ በሚዘረጋው የአስተዳደር መዋቅር ባለው ግዛት ከጫፍ እስከ ጫፍ ያለ ያህል
ሁኖ በመንፈስ የሚተሳሰር አይደለምን? ይልቁን ሰማያዊ ንጉሥ ያከበራቸው የንጉሥ ልጆች ቅዱሳን በእውነተኛ ንጉሣቸው ጸጋ ሰጪነት በሁሉም ቦታ በጸጋ ቢገኙ ወደ
እነርሱ የሚቀርበውን የአማላጅነት ጸሎትን ጨምሮ እርሱ ባወቀ ሌላ ነገርም ይገለጽላቸዋል ቢባል ምኑ የማይታመን ይሆናል? ከዚህም
ሁሉ በላይ እግዚአብሔር በቅዱሳኑ አድሮ ለሚሰራው አሰራር እኛ ካላወቅነው አሰራሩ አይሰራም አልያም የለም ማለት ራስን ማዋረድ፣ በአላዋቂነት
መራመድ ከመሆን ያለፈ ትርጉም አይኖረውም፡፡
በአጸደ ሥጋም ሆነ በአጸደ ነፍስ መላእክትን ጨምሮ እግዚአብሔር ለቅዱሳን የሰጠውን የማማለድን
ጸጋ ዐቅሙን እና አሰራሩን ለማወቅ እንደነርሱ ቅዱስ መሆንን ይጠይቃል፡፡
ቢያንስ እኛ እየወደቅንም እየተነሳንም የቅድስናውን መንገድ እንጀምረው፣ እንመላለስበትም ያኔ
እጃችንን በአፋችን ጭነን፣ በሐሴት እንባ ተውጠን ከመጠየቅ ይልቅ ማድነቅ ምግብ ሲሆነን ከጥያቄ ሊቆጠሩ በማይችሉ ደካማ አስተሳሰቦች
ተይዘን እንደነበረ ይታየናል፡፡
የቅዱሳን ምልጃ ይጠብቀን፡፡