Monday, April 23, 2018

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ማን ነው? (ክፍል ሁለት)


መጥቀስና ማገናዘብ
ቅዱስ መጽሐፍ የሰው ልጅ በጊዜ፣ በቦታ እና ለማስታወስ ካለው ውሱንነት የተነሳ እግዚአብሔር ለሰው ልጆች በቅዱሳን በኩል የሰጠው የሕይወት መመሪያ ነው፡፡ በመጽሐፉ የሰፈረው ቃልም ቃለ እግዚአብሔር ሲሆን ሰዎች የተጻፈውን ተረድተው ሕይወት እንዲያገኙበት ተሰጥቶአል፡፡ በቅዱስ መጽሐፍ ያሉ ቃላተ እግዚአብሔር ዋና ድርሻም በቃልነታችው አማካይነት  የእግዚአብሔርን ሐሳብ፣ ትምህርት፣ ፍቅር፣ ትዕዛዝ…ማድረስ ነው፡፡

ስለዚህም ቃላትን አገኘን ብለን እንደመሰለን ብንተረጉም ሕይወትን ለማሰጠት ከተጻፉ ቃላት ሞትን ልንቀጥፍ እንችላለን፡፡ ጌታችን በዲያብሎስ በተፈተነ ጊዜ መላእክትን ስለ አንተ ያዝልሃል እግርህንም በድንጋይ እንዳትሰናከል በእጃቸው ያነሱሃል ተብሎ ተጽፎአልና የእግዚአብሔር ልጅስ ከሆንህ ወደ ታች ራስህን ወርውር ተብሎ ነበር፡፡ ይህም ከመዝሙር 90፣11-12 የተጠቀሰ እንጂ በቅዱስ መጽሐፍ የሌለ አይደለም፡፡ ይሁንና ቅዱሳት መጻሕፍትን ያጻፈ ራሱ ክርስቶስ ለዚህ መልስ ሲሰጥ አንተ የጠቀስከው ቃል በቅዱስ መጽሐፍ የለም በሚል ሳይሆን  ጌታ አምላክህን አትፈታተነው ተብሎ ደግሞ ተጽፎአል፡፡ በማለት ነው ዘዳ.6፣16፡፡

በዚህም ዲያብሎስ ከቅዱስ መጽሐፍ ሲጠቅስ ጌታችንም ከአንዱ ቅዱስ መጽሐፍ ጠቅሷል፡፡ ነገር ግን የዲያብሎስ ስሕተት የጌታችን ትክክል የሆነው ከቃሉ በቅዱስ መጽሐፍ ተጽፎ አለመገኘትና መገኘት የተነሳ ሳይሆን ቃሉ የያዘውን ሐሳብ በአግባቡ ባለመጠቀምና በመጠቀም (ባለመረዳትና በመረዳት-ማስረዳት) የመጣ ልዩነት ነው፡፡ ማቴ.4፣5-7 በዚህም መሰረት ቅዱሳት መጻሕፍትን በዚሁ አግባብነት እየጠቀሱ እውነቱን መረዳት ይገባል እንጂ እንደ ዲያብሎስ ጥቅስ ስለጠቀሱ ብቻ ትክክል መሆን አይቻልም፡፡ የተሐድሶ አካሄድ ዓላማቸውን ለማሳካት ልክ እንደ ዲያብሎስ ጥቅስ አገኘሁ ብሎ መጥቀስን እንጂ ማገናዘብን፣ መረዳትን፣ ከጌታችን ጀምሮ በሐዋርያት በኩል በትውፊት የተላለፈውን እውነተኛውን መረዳት መከተልን አይደለምና ከስሕተት ይከታል፡፡

ከዚህ ቀጥሎ ተሐድሶዎች ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ማንነት የሚሉት ስሕተትና የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ እንመለከታለን፡፡

ተማላጅ እንጂ አማላጅ አይደለም
ኢየሱስ የእኔ አማላጅ ነው፡፡ ከእርሱ በቀር ሌላ አማላጅ የለኝም አያስፈልገኝም ኢየሱስ በቂዬ ነው የሚሉ ፍጹም ፕሮቴስታንታዊ የሆኑ ትምህርቶችና አገላለጾች በተሐድሶዎች ዘንድ የሚባሉ እና የሚታመኑ ናቸው፡፡ ኢየሱስ በቂዬ ነው ሲባልም በደፈናው ለሚያየው ሰው ትክክለኛ አገላለጽ ሊመስለው ይችላል፡፡ ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያንም ከሚያስፈልገው በላይ ጉዳዮችን የምታበዛ፣ ነገሮችን የምታካብድ፣ አማላጆችን የምትፈጥር የሚመስላቸው የዋሃንም አይታጡም፡፡

አማላጅነት አንድ አካል በራሱ ስልጣን፣ አቅም እና ማንነት ሊያደርገው የማይችለውን ነገር ለሌላ ለሚችል አካል የሚያቀርበውና ካለው ባለሟልነት የተነሳም ተሰሚነት ያለው ልመና ነው፡፡ አማላጅነት ልመና ነው፡፡ ለማኝነት በመሰረታዊነት ሲታይ የማድረግ አቅም ሲታጣ የማስደረግ አቅም ሲኖር የሚደረግ ነው፡፡

ቅዱሳንን አማላጅ የምንለውም በባሕርያቸው አምላክ ያልሆኑ ሁሉን በራሳቸው ስልጣን ማድረግ የማይችሉ ነገር ግን ከእውነተኛው አምላክ ጋር ካላቸው ቀረቤታ( በፍቅሩ በመኖር፣ ሕግን በመፈጸም) የማማለድ ባለሟልነት የተሰጣቸው ስለሆኑ ነው፡፡ የጻድቅ ሰው ጸሎት በሥራዋ እጅግ ኃይል ታደርጋለች። እንዲል ያዕ.5፣16 ከእግዚአብሄር ጆሮ ደርሶ የሚደመጥ መልካም ምላሽን የሚያስገኝ ጸሎት ማናችንም የምንጸልየው ጸሎት ሳይሆን ጻድቃን በአጠቃላይ ቅዱሳን የሚጸልዩት ጸሎት መሆኑን ያስረዳል፡፡ ይህም ሲባል እኔ ቅዱስ አይደለሁምና መጸለይ አይገባኝም የሚያስብል ሳይሆን የቅዱሳን ምልጃ ያስፈልገኛል እግዚአብሔር ያመለከተው መንገድ ነው የሚያስብልና በዚያ እንድንጸና የሚረዳ ነው፡፡ የቅዱሳኑ የመቀደስ፣ ጻድቅ የመሆን መንገዱም ይኸው ራሱ ነውና፡፡
                                                     
ፍጹም አምላክ ብቻ ሳይሆን ፍጹም ሰውም ነውና ያለቀሰ፣ የተራበ፣ የደከመ ሲሆን፣ የሚሞት ሥጋን ተዋሕዶ ሰው መሆኑን ለማስረዳት፣ በሌላም በኩል በአዳም/በእኛ በበደልነው በሰው ልጆች ቦታ ሆኖ እኛ የምንለምነውን ልመና፣ የምናነባውን እንባ በማቅረቡ ለመነ አማለደ የሚሉ ቃላቶችን እናገኛለን፡፡ እኔ ግን እምነትህ እንዳይጠፋ ስለ አንተ አማለድሁ፤ አንተም በተመለስህ ጊዜ ወንድሞችህን አጽና አለ። ሉቃ.22፣32 እርሱም በስጋው ወራት ከሞት ሊያድነው ወደሚችል ከብርቱ ጩኸትና ከእንባ ጋር ጸሎትንና ምልጃን አቀረበ፥ እግዚአብሔርንም ስለ መፍራቱ ተሰማለት፤ዕብ.5፣7 ማለቱም ለዚህ ነው፡፡

የእነዚህ ቃላት ዓላማ ግን ራሱ አምላክ ሳይሆን ቀርቶ፣ አቅም ያጣ ሆኖ እንደሚለምን ለማመልከት አይደሉም፡፡ ምክንያቱም እርሱ ሌላ ሰጪ፣ ቀዳሚ የሌለው እግዚአብሔር፣ አምላክ፣ ፈጣሪ መሆኑ ተጠቅሷልና፡፡ ሮሜ 9፣5፣ ኤፌ.2፣10 ሁል ጊዜ የምንጠቅሰው በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ አንድ ቁጥር አንድ ላይ በመጀመሪያው ቃል ነበረ፥ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፥ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ። በማለት ቁጥር 14 ላይ ሥጋን መዋሐዱን የተናገረለት ያ ቃል ኢየሱስ ክርስቶስ እንደሆነ በግልጽ ይመሰክራልና፡፡ ሰው በመሆኑ እግዚአብሔር መሆኑ አልቀረምና፤ ታዲያ እግዚአብሔር ጸለየ፣ አማለደ ተብሎ ቢነገር ፍቺው ምንድነው? ስለዚህ ዋና ሐሳቡን ትቶ አማላጅ ማለት ከመጽሐፍ ቅዱስ ሐሳብ ያስወጣናል፡፡

ተግባሩ ካለ መቻል የተነሳ ሳይሆን ከመቻል የተነሳ የማዳን ሂደት ነውና አቅም እንዳጣ አማላጅ የሚለው ቅጽል እና ሐሳብ አይመጥነውም፡፡ ምንም እንኳ ነገሮች ከመሆናቸው በፊት የሚያውቅ፣ ለነቢያትም ሀብተ ትንቢትን የሰጠ ቢሆንም ትንቢትን የሚናገር ከመሆኑ የተነሳ ነቢይ ማለት ለፍጡራን የሰጠውን የነቢይነት ማዕረግ እንደሚያስመስለውና ከአምላክነት አንጻር ነቢይ ብሎ መጥራቱ ዝቅታ በመሆኑ ነቢይ እንደማንለው ሁሉ፡፡

በሌላ በኩል እርሱ ከአብ የሚቀበል፣ የሚያንስ አድርገው የሚያስቡ ወገኖች የሚከተሉትን ጥቅሶች አንብቡ ቢባሉ በጥድፊያ ይዘልቋቸዋል፡፡ ሥልጣን ሁሉ በሰማይና በምድር ተሰጠኝ። ማቴ.28፣18፣ የሰውን ልጅ ከፍ ከፍ ባደረጋችሁት ጊዜ እኔ እሆን ዘንድ አባቴም እንዳስተማረኝ እነዚህን እናገር ዘንድ እንጂ ከራሴ አንዳች እንዳላደርግ በዚያን ጊዜ ታውቃላችሁ። ዮሐ.8፣28፣ እኔ በፈቃዴ አኖራታለሁ እንጂ ከእኔ ማንም አይወስዳትም። ላኖራት ሥልጣን አለኝ ደግሞም ላነሣት ሥልጣን አለኝ ይህችን ትእዛዝ ከአባቴ ተቀበልሁ። ዮሐ.10፣18 ተሰጠኝ፣ አባቴ እንዳስተማረኝ፣ ከራሴ አንዳች እንዳላደርግ፣ ትእዛዝ ከአባቴ ተቀበልሁ…፡፡ እነዚህ አገላለጾች አይሁድ አብን እናውቃለን፣ እግዚአብሔር አባታችን ነው፣… ይሉ ስለነበር ከአብ አለመለየቱን፣ እንዲያውም ፈጽሞ በአብ ዘንድ ያለ መሆኑን፣ አብን እናውቃለን ባዮች እርሱን(ወልድን) አለማወቃቸው የሚያስደንቅና ያልተገባ መሆኑን፣ አብን የማወቅ መስፈርቱ ወልድን ማወቅ፣ ወልድንም የማወቅ መስፈርቱ አብን ማወቅ መሆኑን ለማስረዳት እንጂ እርሱ አቅም የሌለው ፣ ከሌላው የሚቀበል መሆኑን ለመግለጽ እንዳልሆነ ማስተዋል ይገባል፡፡

ከአብ በቀር ወልድን የሚያውቅ የለም፥ ከወልድም በቀር ወልድም ሊገለጥለት ከሚፈቅድ በቀር አብን የሚያውቅ የለም። ማቴ.11፣27 እንዲል፡፡ ዳግመኛም እንዲህ ብሏል፡፡ እንግዲህ። አባትህ ወዴት ነው? አሉት። ኢየሱስ መልሶ፦ እኔንም ወይም አባቴንም አታውቁም፤ እኔንስ ብታውቁኝ አባቴን ደግሞ ባወቃችሁ ነበር አላቸው። ዮሐ.8፣19 እግዚአብሔርስ አባታችሁ ከሆነ በወደዳችሁኝ ነበር፤ እኔ ከእግዚአብሔር ወጥቼ መጥቻለሁና፤ እርሱ ላከኝ እንጂ ከራሴ አልመጣሁምና። ዮሐ.8፣42 አይሁድ አባታችን እግዚአብሔር ነው ብለው ስለተከራከሩት በተግባር የእግዚአብሔር ልጆች ሆነው ቢሆን ኖሮ ክርስቶስን ለመግደል ሊፈልጉት ቀርቶ ሊወድዱት ይገባ ስለነበር እርሱ ከአብ ዘንድ አይደለም በሚል እርሱን ላለመቀበል ምክንያት እንዳይሆናቸው ከራሴ አልመጣሁም፣ ያ አባታችን የምትሉት ላከኝ በሚሉ አገላለጾች ሁሉን ለአብ ሰጥቶ ተናግሯቸዋል፡፡ ይህም ማለት ወልድ ከአብ የተለየ ፈቃድ እንደሌለው፣ በፈቃድ አንድ እንደሆኑ፣ የፈቃድ አንድነታቸውንም ከራሴ አልመጣሁም አብ ላከኝ በማለት የአብ ተቃራኒ እና አብን የማያውቅ፣ አብ የማያውቀውና በራሱ ፍላጎት ብቻ የተገለጸ አድርገው ማሰባቸው ስሕተት እንደሆነ ሲያሳይ ነው፡፡

እንዲህማ ባይሆን ኖሮ በማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ አምስት ላይ እንደተገለጸው በገዛ ስልጣኑ ሕግን እንዴት ይሰራ ነበር? ራሱን ከአብ ጋር በስልጣን አንድ አድርጎ እኔና አብ አንድ ነን፣ እኔን ያየ አብን አየ…እንዴት ይላቸው ነበር? ዮሐ.10፣30፤ ዮሐ.14፣6-12፡፡ የኋላ ኋላ አይሁድ ሊገድሉት የፈለጉትስ ራሱን እግዚአብሔር አድርጓል በሚል አልነበረምን? ኢየሱስ፦ ከአባቴ ብዙ መልካም ሥራ አሳየኋችሁ፤ ከእነርሱ ስለ ማናቸው ሥራ ትወግሩኛላችሁ? ብሎ መለሰላቸው።  አይሁድም። ስለ መልካም ሥራ አንወግርህም፤ ስለ ስድብ፤ አንተም ሰው ስትሆን ራስህን አምላክ ስለ ማድረግህ ነው እንጂ ብለው መለሱለት። እንዲል ዮሐ. 10፣32-33

ከላይ እንደተመለከተው አንድ ካህን(ቄስ) በትህትና በዲያቆን ቦታ ሆኖ ቢቀድስ እርሱ ዲቁና እንጂ ቅስና የለውም ማለት ሞኝነት እንደሆነ ሁሉ ከማዳኑ ስራው ተነስቶ ኢየሱስ ክርስቶስን አማላጅ ማለት የተሳሳተ የማንነት ትምህርት ነው፡፡

ከትንሳኤ በኋላም ቢሆን ጌታችን ተፈጸመ ኩሉ ብሎ ከእንግዲህ በኃይል ለፍርድ እንጂ በትህትና እንደማይገለጽ ነግሮናል፡፡ ከዚህ በኋላ ኢየሱስ አሁን ሁሉ እንደተፈጸመ አውቆ የመጽሐፉ ቃል ይፈጸም ዘንድ። ተጠማሁ አለ።…ኢየሱስም ሆምጣጤውን ከተቀበለ በኋላ። ተፈጸመ አለ፥ ራሱንም አዘንብሎ ነፍሱን አሳልፎ ሰጠ። ዮሐ.19፣28-30፤ ማቴ.26፣64 እነዚህ ወገኖች ስለ እነርሱም ሊያምልድ ዘወትር በሕይወት ይኖራልና ስለዚህ ደግሞ በእርሱ ወደ እግዚአብሔር የሚመጡትን ፈጽሞ ሊያድናቸው ይችላል። ዕብ.7፣25 የሚለውን ገጸ ንባብ ጠቅሰው ከትንሳኤ በኋላም አማላጅ ነው ለማለት ይደፍራሉ፡፡ የጥቅሱ ሐሳብ ግን ክርስቶስ ያቀረበው የቀራንዮ ቤዛነት አንድ ጊዜ የተፈጸመ ለዘላለም የሚሰራ መሆኑን ለማመልከት እንጂ እነርሱ እንደሚሉትስ አይደለም፡፡ እርሱም እንደነዚያ ሊቃነ ካህናት አስቀድሞ ስለ ራሱ ኃጢአት በኋላም ስለ ሕዝቡ ኃጢአት ዕለት ዕለት መሥዋዕትን ሊያቀርብ አያስፈልገውም፤ ራሱን ባቀረበ ጊዜ ይህን አንድ ጊዜ ፈጽሞ አድርጎአልና። ዕብ.7፣27 ስለሚልባቸው፡፡

በእኛ ተገብቶ ያቀረበው ልመናውም ቢሆን ከትንሳኤው በፊት የፈጸመው ነው እንጂ አሁን የሚያደርገው አይደለም፡፡ አሁንማ በቀኝ ተቀምጧል በግርማ ለፍርድ ይመጣል፤ ታድያ አሁን ላይስ ቢሆን እንዴት አማላጅ ተብሎ ሊጠራ ይችላል፡፡ ማር.16፣19፤ ራዕ.1፣7

አምላክ ሆኖ አማላጅ መሆን ትርጉም አለውን?
ቅዱሳት መጻሕፍት ለኑፋቄአቸው መንገድ ሲያሳጧቸው አንዳንዶቹ የሚሉት ደግሞ አምላክም አማላጅም ነው የሚል ነው፡፡ አምላክነቱ እንዳለ ሁኖ አማላጅ ነው እያልን ነው ቢሉ እንኳ በአንድ በኩል አምላክነትና አማላጅነት የሚቃረኑና አብረው የማይሄዱ ሲሆን(አምላክ ከሆነ ማንን፣ እንደምን ይለምናል? አማላጅስ ከሆነ እንዴት ሁሉን ማድረግ የሚችለውን ባሕርይ እንዳለው አምላክ ይባላል?) በሌላ በኩል ደግሞ በእውነት እንደዚህ የሚሉ ቢሆኑ ስለ አምላክነቱ መቼ ሰበኩ? እርሱንስ በፍጡር የሚደረገውን ተግባር እንደሚሰራ ቆጥረው አማላጅ የማይሉት ቢሆን ኖሮ እንዴት የቅዱሳንን አማላጅነት አስቀሩ? የቅዱሳንን ተግባር ለእርሱ ሰጥተው አማላጅ ስለሚሉት አይደለምን!
አምላክነትን ያላስቀማ አማላጅነት ነው ያለው ካሉን ደግሞ ይህስ አስታራቂነት፣ መሐሪነት የሚለው አገላለጽ ይስማማዋል እንላለን፡፡ ማስታረቁም ከራሱ፣ ከአባቱ ከአብ፣ ከሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ ለምሳሌ እግዚአብሔር ኑ እንዋቀስ ብሎ ሲለምነን በመሰረታዊነት ለማኝ የሚል ማንነት ሳይሆን መሐሪ፣ ይቅር ባይ፣ አዳኝ የሚለው ማንነት ይገልጸዋል፡፡ ልመናው የማድረግ ስልጣን፣ ባሕርይ ከማጣት ሳይሆን ካለው መሐሪነት ስለመሆኑ የሚያስረዳ ነውና፡፡ ኢሳ.1፣18 ደግሞም እንግዲህ እግዚአብሔር በእኛ እንደሚማልድ ስለ ክርስቶስ መልክተኞች ነን፤ ከእግዚአብሔር ጋር ታረቁ ብለን ስለ ክርስቶስ እንለምናለን። በሚለው እግዚአብሔር…እንደሚማልድ ብሎ እኛን አንደሚለምነን ያሳያል፤ ነገር ግን ሐሳቡን እንጂ ቃሉን ብቻ አንመለከትምና  አእምሮ እንዳጣ ሰው ሆነን እግዚአብሔርን ለማኝ፣ አማላጅ የምንለው ሳይሆን እንደባለ አእምሮ ሰው ሆነን ምሕረቱ የበዛ፣ መሐሪ፣ አዳኝ እንለዋል፡፡

ወልደ እግዚአብሔር ሕያው
እንግዲህ ይህንን ታላቅ የማንነት ጥያቄ ከአይሁድ ባሻገር ራሱ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጠይቆ ትክክለኛውን መልስም ነግሮናል፡፡ በፊልጶስ ቂሣርያ ሰዎች የሰውን ልጅ ማን ይሉታል ብሎ ሐዋርያትን በጠየቀ ጊዜ አንዳንዱ መጥምቁ ዮሐንስ፥ ሌሎችም ኤልያስ፥ ሌሎችም ኤርምያስ ወይም ከነቢያት አንዱ እንደሚሉት ነግረውት ነበር፡፡ ጌታችንም እናንተስ እኔን ማን እንደሆንሁ ትላላችሁ ሲላቸው ቅዱስ ጴጥሮስ እንዲህ አለ፡፡ አንተ ክርስቶስ የሕያው የእግዚአብሔር ልጅ ነህ፡፡ ጌታችንም የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ፥ በሰማያት ያለው አባቴ እንጂ ሥጋና ደም ይህን አልገለጠልህምና ብፁዕ ነህ። እኔም እልሃለሁ፥ አንተ ጴጥሮስ ነህ፥ በዚችም ዓለት ላይ ቤተ ክርስቲያኔን እሠራለሁ፥ የገሃነም ደጆችም አይችሉአትም። ብሎታል፡፡ የእግዚአብሔር ልጅ መባሉ እንደ ሰዎች በመሰለ ልደት አይደለም፡፡ ከፍጥረታት በፊት(ጊዜን ጨምሮ) ያለ እናት የተወለደው የማይመረመር ልደት ነውና መበላለጥ ፣ መቀዳደም የሌለበት፣ አንዱ ሰጪ ሌላው ተቀባይ ያልሆነበት ስለሆነ ራሱ የእግዚአብሔር ልጅ እግዚአብሔር ነው፡፡ ለዚህም ነው በምሥጢረ ሥላሴ ትምህርት አብ፣ ወልድ፣ መንፈስ ቅዱስ ሦስት አካላት፣ ሦስት ስሞች፣ ሦስት ግብራት አንድ እግዚአብሔር የምንለው፡፡ እግዚአብሔርን አማላጅ ማድረግም እብደት ነው፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር፣ ስብሐት ለማርያም፣ ስብሐት ለመስቀለ እግዚእነ

Monday, April 9, 2018

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ማን ነው? (ክፍል አንድ)


የሰው ልጅ ከሚያነሳቸው ጥያቄዎች ሁሉ ለፍለጋ ከማነሳሳት እና እውነትን ከመግለጥ አንጻር ፋይዳው ከፍ ከሚሉት አንዱ የማንነት ጥያቄ ነው፡፡ በርግጥ ማን ነህ? ማን ነሽ? የሚሉ ጥያቄዎች ለሰው ልጅ ሲቀርቡ በቀበሌ መታወቂያቸው ላይ የሰፈረውን መረጃ መጥቀሱ መልስ ሊሆን ይችላል፤ እዚያ ላይ ሙሉ ስም፣ ጾታ፣ ዜግነት፣ የትውልድ ቦታ፣ ዕድሜ፣ ሥራ፣ የትዳር ሁኔታ፣ ቀበሌ፣ የመኖሪያ ቤት ቁጥር፣ የስልክ አድራሻ…  ተጠቅሰዋልና፡፡ ሰዎችም የሰዎችን መታወቂያ በማየት ስለ እነዚያ ሰዎች ከላይ የተጠቀሱትን ግንዛቤዎችን ያገኛሉ፤  መታወቂያው ሐሰተኛ ካልሆነ፡፡

ይህ ሁሉ መረጃ ግን የማንነት መገለጫ ተደርጎ ሊወሰድ የቻለው አስቀድሞ አንድ ትልቅ የማንነት ጥያቄ ምላሽ በማግኘቱ ነው፡፡ ይኸውም “ማን ነው?” የሚለው ጥያቄ “ሰው ነው” የሚል መልስ ስላገኘ፡፡ እናም መታወቂያው ሰው ለመሆናችን ምክንያት ባይሆንም ሰው መሆናችንን ይመሰክራል፡፡ የአንድን አካል ማንነት በአግባቡ አለማወቅም ለስህተት ይዳርጋል፤ በተለይ የዚያ አካል ማንነት በሌሎቹ ላይ የሚኖረው ድርሻ ትርጉሙ ከፍ ያለ ሲሆን፡፡

አንድ ለማንነት እውቅና የሚሰጥ አካል ለአንድ ሰው ፍጥረቱን ዝቅ አድርጎ ዝንጀሮ የሚል ማንነት ቢሰጠው ወይም አኗኗሩን ከፍ አድርጎ መልአክ የሚል ማንነት ቢሰጠው ይህ የተሰጠው አዲስ ማንነት ሰውዬዉን ብቻ ሳይሆን በአካባቢው ላሉ ፍጥረታት በሙሉ ተጽዕኖ ይኖረዋል፡፡ ሰውን ዝንጀሮ የሚል ማንነት ሲሰጡት በአኗኗሩ እንደ ዝንጀሮ በዱር ወይ በፓርክ ውስጥ፣ ጋብቻው ከዝንጀሮ ጋር እንዲሆን ይጠበቃል፣ ሰው ስለመሆኑ እውቅና አልሰጠውምና በሥጋ ያሉት ዘመዶቹ እንዲለዩት … ሲሆን መልአክ የሚል ማንነት ሲሰጡት ደግሞ የቀበሌ ስኳርና ዘይት ብቻ ሳይሆን ከነአካቴው ምግብ አያስፈልገውምና አይብላ፣ መጓጓዣ ኣያስፈልገውም፣… አይሳሳትም፣ …ተብሎ ይቆጠራል፡፡

ስለዚህም የማንነት ጥያቄ ታላቅ የሚሆነው በአንድ በኩል ትክክለኛ ምላሽ ሲያገኝ እውነትን የምናውቅበት መንገድ ስለሆነ ሲሆን በሌላ በኩል ደግም ትክክለኛ ምላሽ ሳያገኝ ሲቀር ከእውነት ፈጽሞ የምንርቅበት እና የምንጠፋበት ስለሆነ ነው፡፡

በቅዱስ መጽሐፍ ውስጥ የማንነት ጥያቄዎች ሲነሱ እና ምላሽ ሲሰጣቸው እንመለከታለን፡፡ ከምላሽ ሰጪው አካል ወይ ከጠያቂው አካል እውነተኛነት፣ ፍላጎት፣ እውቀትና ዝግጁነት የተነሳም የተለያዩ ምላሾች ተሰጥተዋል፡፡ ከዚህም ሌላ ጥያቄ ያልቀደማቸው ምስክርነቶችም አሉ፡፡

መነ ትብል ርእሰከ?
መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ አይሁድ ስለ ማንነቱ በጠየቁት ጊዜ የሰጠው ምላሽ እኔ ክርስቶስ አይደለሁም የሚል ነው፡፡ ዮሐንስ በምድረ በዳ ያደገ፣ በብህትውና የኖረ፣ ሰዎችን በውሀ የንስሐን ጥምቀት ሲያጠምቅ የነበረ በመሆኑ ለብዙዎቹ ክርስቶስ መስሎአቸው ነበርና ስለ ማንነቱ ከራሱ ለመረዳት ካህናትንና ሌዋውያንን ልከውበት ነበረ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም መልስ መስጠት የጀመረው እርሱ ማን እንደሆነ በመግለጽ ሳይሆን ማን እንዳልሆነ በመግለጽ ነው፡፡ ይህም ስለርሱ ማንነት በብዙዎች ዘንድ ያለው አረዳድ ክርስቶስ ነው የሚል የተሳሳተ ስለነበረ ያልሆነውን አይደለሁም በማለት መልስ ሰጥቶአል፡፡ ይህም እንደ ትልቅ ተጋድሎ ተቆጥሮለት መሰከረም አልካደምም እኔ ክርስቶስ አይደለሁም ብሎ መሰከረ ተብሎ ተጽፎለታል፡፡ በርግጥ ታላቅ ምስክርነት ነበረ፡፡ ከዮሐንስ ተግባራትና አኗኗር አንጻር ክብር ይግባውና እንደ ሐሰተኞቹ ምድራዊ ስም፣ ዝናና ክብር ለማግኘት ሲል ሐሰተኛ ማንነትን ለራሱ ደርቦ እርሱ ክርስቶስ ነኝ ቢል ብዙዎች ይከተሉት ነበር ፡፡  ክርስቶስን የሚመስል(በመንገዱ) እርሱ ይቅርና ክርስቶስን ከቶ የማይመስሉ የዘመናችን ሆድ እና ስሜት አምላኪ ሐሰተኛ መምህራንም ቲፎዞ ሲያሰባስቡ እናያለንና፡፡ በዚያ ላይ ከርሱ ማረጋገጫን የሚጠብቁ( ክርስቶስ አይደለሁም እንዲል ሳይሆን ነኝ እንዲል የሚጠብቁ) ብዙ ተከታዮች በነበሩበት ጊዜ፡፡

ነገር ግን የቅዱሳን አንዱ እና ቀዳሚው መገለጫ እውነተኛነት ስለሆነ ያልሆኑትን እና የማይገባቸውን ማንነት/ክብር አብዝተው ይርቁታል በቁርጠኝነትም አይገባንም ብለው ትህትናን በሚቀድም እውነታ ይመሰክራሉ፡፡ እርሱ ክርስቶስ ካልሆነ ስለ ራሱ ማንነት እንዲናገር በተጠየቀ ጊዜ በነቢዩ ኢሳይያስ ስለ እርሱ የተጻፈውን በመጥቀስ የጌታን መንገድ አቅኑ እያለ በምድረ በዳ የሚጮኽ ድምጽ እኔ ነኝ የሚልን ምላሽ ሰጥቶአል፡፡ የክርስቶስን ማንነት ከራሱ ማንነት ጋር ሲያነጻጽርም የጫማውን ጠፍር ልፈታ የማይገባኝ፣ ከእኔ በፊት የነበረ ከእኔ በኋላ የሚመጣ በሚሉ ሐረጎች ገልጾታል፡፡ዮሐ. 1፣19-27

ሰዎችን መስለው ወርደዋል
ሐዋርያት ከእግዚአብሔር ባገኙት ጸጋ ትምህርቱን ከተአምራት ጋር ያስተምሩ ነበር፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም ከበርናባስ ጋር ሆኖ በልስጥራን ለአገልግሎት በተገኘበት ጊዜ ቃለ እግዚአብሔርን በማስተዋል ይሰማ የነበረና እምነት የነበረው ከእናቱ ማሕጸን ጀምሮ አንካሳ የነበረ ሰው ቅዱስ ጳውሎስ በታላቅ ድምጽ ተነሳ ባለው ጊዜ ቀጥ ብሎ በመነሳት ተመላልሷል፡፡ ይህን ያዩ ህዝቡም አማልክት ሰዎችን መስለው ወርደዋል በማለት ለጳውሎስና በርናባስ ሄርሜንና ድያ የሚሉ የጣኦታትን ስሞችን ሰጧቸው፤ ካህነ ጣኦታትም መስዋእትን ይሰዋላቸው ዘንድ ኮርማዎችን ይዞ መጣ፡፡

ህዝቡ ካዩት ተአምራት በመነሳት ቅዱስ ጳውሎስንና በርናባስን መጠየቅ ሳያሻቸው ማንነታቸውን አማልክት በማለት ገልጸውታል፡፡ ዝናን፣ ክብርንና ሐሰትን በሚፈልግ በዚህ ዓለም ዘንድ አምላክ መባልና ተከታይ ማግኘት እጅግ የሚፈለግ ቢሆንም በሐዋርያት ዘንድ ግን የሐሰት ማንነት ሞት በመሆኑ የተጸየፉትና በጩኸትም ሳይቀር አምርረው የተቃወሙት ነበር፡፡ በብዙ ጭንቅም እነርሱን አማልክት በሚል የተሳሳተ ማንነት እንዳያመልኳቸውና እንዳይሰዉላቸው አድርገዋል፡፡ በሌላም በኩል የእውነተኛውን አምላክ ማንነት አስተምረዋቸዋል፡፡ ሐዋ.14፣ 11-15

ጌታችንን በተመለከተ የቀረቡ የማንነት ጥያቄዎችና የሰዎች አረዳዶች
ራሱ መድኅነ ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ ሲያስተምር በነበረበት ጊዜ ስለ ራሱ ማንነት ከአይሁድም ከራሱም ጥያቄ ቀርበዋል፡፡ አይሁድ ስለ ክርስቶስ ማንነት የነበራቸው አረዳድ ትክክል አለመሆኑ ብቻ ሳይሆን ከእነርሱ በተሻለ ሁኔታ የተረዱትን እንኳ መረዳታቸውን ሲኮንኑ ነበር፡፡

ከመወለዱ ጀምሮ ዕውር የነበረውን ሰው ጌታችን ባዳነው ጊዜ አይሁድ እግዚአብሔርን አክብር ይህ ሰው ኃጢአተኛ መሆኑን እናውቃለን በማለት ስለ ክርስቶስ ማንነት በጠየቁት ጊዜ ኃጢአተኛ መሆኑን አላውቅም ዕውር እንደነበርሁ አሁንም እንዳይ ይህን አንድ ነገር አውቃለሁ ብሏቸዋል፡፡ ይልቁንም መምህራን ነን ባዮቹን ስለ ክርስቶስ ማንነት አለማወቃቸውን እንዲህ ሲል በአድናቆት ይናገራቸዋል፡፡ ከወዴት እንደሆነ እናንተ አለማወቃችሁ ይህ ድንቅ ነገር ነው፤ ዳሩ ግን ዓይኖቼን ከፈተ፡፡ ዮሐ.9፣1-30

አንተ ማን ነህ ? ዮሐ.8፣25
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ራሱ ማንነት እና ስለ አይሁድ ማንነት ሲናገር ይህ ያልተዋጠላቸው ፈሪሳውያን መልስን ሳይሹ ጠይቀውታል፤ መልስን ፈልገው ቢሆን ኖሮ በተለያዩ ጊዜያት የነገራቸውን እና ያደረጋቸውን ያስተውሉ እና ይረዱ ነበርና፡፡ ይሁን እንጂ ስለ ክርስቶስ ትክክለኛ ማንነት ከመረዳት ይልቅ እርሱ እንዲኖረው የሚፈልጉትን የፍጡርን እና የኃጢአተኛን ማንነት ይሰጡት ነበር፡፡ እንግዲህ አንተ ማነህ? ለሚለው ጥያቄአቸውም ከመጀመሪያ ለእናንተ የተናገርሁት ነኝ የሚል ምላሽ ሰጥቶአቸዋል፡፡

ራስህን ማንን ታደርጋለህ ? ዮሐ.8፣53
እውነት እውነት እላችኋለሁ ቃሌን የሚጠብቅ ቢኖር ለዘላለም ሞትን አያይም፡፡ የሚለውን የጌታችንን ትምህርት ተከትሎ አይሁድ ነገሩ እውነትነት የሌለው አድርገው በመቁጠር በስላቅ የጠየቁት ነው “ራስህ ማንን ታደርጋለህ?” የሚለው፡፡ ለዚህም ማሳያ እንዲሆናቸው የሚከተለውን አመክንዮ ተጠቅመዋል፡፡ የያዙት አመክንዮም በእነርሱ አረዳድ እጅግ ጠንካራና እውነት አድርገው ስለወሰዱት ስድብን አስቀድመው አመክንዮአቸውን አስከትለው አቅርበዋል፡፡  ጋኔን እንዳለብህ አሁን አወቅን ብለው ሲያበቁ ምክንያታቸውንም አብርሃም ስንኳ ሞተ ነቢያትም …በውኑ አንተ ከሞተው ከአባታችን ከአብርሃም ትበልጣለህን? ነቢያትም ሞቱ ራስህን ማንን ታደርጋለህ? ይሉታል፡፡  ጌታችንም አባታችሁ አብርሃም ቀኔን ያይ ዘንድ ሐሴት አደረገ አየም ደስም አለው ባላቸው ጊዜ አይሁድ ገና ሃምሳ ዓመት ያልሆነህ አብርሃምን አይተሃልን? ብለውታል፡፡  ጌታችንም እውነት እውነት እላችኋለሁ አብርሃም ሳይወለድ እኔ አለሁ ብሎ ትክክለኛ ማነነቱን ቢነግራቸው ከአመክንዮአቸው የሚልቀውን እውነት ላለመቀበል ሊወግሩት ድንጋይ አነሱ፡፡

ይህንን የመሰሉ ክርስቶስን የተመለከቱ የማንነት ጥያቄዎች በቅዱስ መጽሐፍ በርካታ ጊዜ ተነስተዋል፡፡ ክርስቶስ አንተ ነህን ንገረን ሉቃ.22፣67፤ ዮሐ.10፣24፤ ከአንዱ ከእግዚአብሔር በቀር ኃጢአትን ሊያስተሰርይ ማን ይችላል ማር.2፣7 የሚሉትን መመልከት ይቻላል፡፡

የማንነት ጥያቄ ታልቅ ከመሆኑ የተነሳ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በኦርቶዶክሳዊነታቸው የምትቀበላቸው ሦስቱ ዓለም አቀፍ ጉባኤያት ማለትም ጉባኤ ኒቂያ፣ ጉባኤ ቁስጥንጥንያ እና ጉባኤ ኤፌሶን የማንነት ጥያቄዎችን ለመመለስ የተጠሩ ነበሩ፡፡ በጉባኤ ኒቂያ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ማንነት ተነስቶ ከአብ ጋር አንድ የሆነ አምላክ፣ በጉባኤ ቁስጥንጥንያ ስለ መንፈስ ቅዱስ ማንነት ተነስቶ ከአብ የሰረጸ አምላክ፣ በጉባኤ ኤፌሶን ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ እና ድንግል ማርያም ማንነት ተነስቶ ድንግል ማርያም ወላዲተ አምላክ የሚሉ ምስክርነቶች ከቅዱሳት መጻሕፍት በመሰጠቱ እና ይህንንም እውነታ በውሳኔ በማጽናታቸው ነው፡፡

የአይሁድ ስሕተት
አዋቆች ነን ባዮቹ ጸሐፍት፣ ፈሪሳውያን በአጠቃላይ አይሁድ ስለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ማንነት መሰረታዊ ስህተት ውስጥ የወደቁት ከሚያጣቅሷቸው መጻሕፍት አግባብ አለመሆን አልነበረም፡፡ ነገር ግን በእነርሱ ዘንድ ያለውን በቅዱሳት መጻሕፍት የተገለጠውን እውነታ አንድም በአግባቡ ባለመረዳት አንድም ለራሳቸው ምድራዊ ክብር በሚያመች ሁኔታ ሲተረጉሟቸው ስለ ነበር ነው፡፡ ጌታችንንም ጋኔን ያለበት፣ የዮሴፍ ልጅ፣ ኃጢአተኛበሚሉ አይደለም ለክርስቶስ ለአንድ ተራ ሰው እንኳ ቢቀጸሉ ተገቢ ያልሆኑ አገላለጾችን ተጠቅመው ጠርተውታል፡፡ ይሁንና ጌታችን ይድኑ ዘንድ እውነቱን አብዝቶ ነገራቸው እንጂ አላራቃቸውም፡፡  እኔ ግን እውነትን የምናገር ስለሆንሁ አታምኑኝም ከእናንተ ስለ ኃጢአት የሚወቅሰኝ ማነው? እውነት የምናገር ከሆንሁ እናንተ ስለምን አታምኑኝም? እንዲል ዮሐ.8፣45-46 ደግሞም እኔስ ጋኔን የለብኝም… እናንተም ታዋርዱኛላችሁ ብሏል፡፡ ቁ.49 ከሁሉ አስቀድሞ በብዙ መንገድ ለድኅነት የተጠሩት አይሁድ ቢሆኑም ስለ ክርስቶስ ማንነት ሳይረዱ ቀርተው ከፊሎቹ ከተስፋው ወጥተዋል፡፡

አረዳዳቸውና ድርጊታቸውም ራሱ ዕውር ሆኖ ብርሃንን የሚሻውን ዕውርን እንምራህ እያሉ ተያይዘው ገደል ገብተዋል፡፡ ማቴ.15፣14 በዮሐንስ ወንጌል ላይ እንደተጻፈውም እውነትን ከመረዳት ውጭ ሆነው ስለ ክርስቶስ ማንነት መረዳት ተስኗቸው ነበር፡፡ ስለዚህም ጌታችን እንዲህ አላቸው እናንተ በመጻሕፍት የዘላለም ሕይወት እንዳላችሁ ይመስላችኋልና እነርሱን ትመረምራላችሁ፤ እነርሱም ስለ እኔ የሚመሰክሩ ናቸው ነገር ግን ሕይወት እንዲሆንላችሁ ወደ እኔ ልትመጡ አትወዱም። ዮሐ.5፣39-40

በዚህ በዘመናችንም በእነርሱ ዘንድ እውነት እንደሌለ ቢያውቁት ሳይጠሯቸው እና ሳያገባቸው እናት ያልሆነቻቸውን እውነት የያዘችውን ቅድስት ቤተክርስቲያንን እናድሳት እያሉ በከንቱ ይቀባጥራሉ፡፡ በእውነት ክቡር ሆኖ የተፈጠረ የሰው ልጅም እንዲህ ባለ ከንቱ ስራ ሲሰማራና በግድ ጨምሩኝ ብሎ በሌለው እውነት፣ ሊቅነትና ቅድምና ሲዳክር፣ ምእመናንን የዲያብሎስ ምርኮኛ ሀገርን ዘመናዊ ቅኝ ተገዢ እንድትሆን ሲሰራ ማየት ያማል፡፡ ለመዳን ጨምሩኝ ብለው ቢሆንስ ባልከፋ የቤተክርስቲያን ዓላማ ሰዎችን ለድኅነት መጥራት ነውና፡፡ ነገር ግን እነርሱ የአባታቸው የዲያብሎስ ደቀመዛሙርት ሆነው ክርስቶስ ራሷ የሆነውን ቅድስት ቤተክርስቲያንን ይታገላሉ፤ ለዚህም ነው ሰልፉ መንፈሳዊ ሰልፍ የሚሆነው፡፡

“በአንድ ቤተ እምነት ተግኝቶ አንድ ሰው የተናገረው” በሚል ነጣቂ ተኩላነታቸውን በመመስከር በተሐድሶ መጽሔት ላይ የሰፈረው  “…ከእንግዲህ ሰውን ከዓለም እንጂ ከቤተ ክርስቲያን አናወጣም፡፡ ወደ ጤናማነት እንመለሳለን እንጂ ከእንግዲህ ወደ እብደት አንሄድም፡፡” ብሎ ነበር፡፡ ይሁንና ይህንን የሚልበትን አስተሳሰብ ስንመለከት በአንድ በኩል “ሁሉም አብያተ እምነት ያድናሉ” ከሚል አደገኛ እና ፈጽሞ ስሑት የሆነ አስተሳሰብ ሲሆን በሌላ በኩል ደግም በየቤተ እምነታቸው እንዳሉ ሆነው መርዛቸው እንዲረጩ በማሰብ መሆኑን ያስታውቃል፡፡ “ከሌላው የተነጠቁ ምእመናን ሁሌም የእናንተ አይደሉም፤ የዚህ ሰው ፈውስ ያለው በቤተ ክርስቲያኑ ነው፡፡ ስለዚህ ሙሉ ወንጌል የሆነውን ወደ ሙሉ ወንጌል፣ መሠረተ ክርስቶስ የሆነውን ወደ መሠረተ ክርስቶስ፣ ኦርቶዶክስ የሆነውን ወደ ኦርቶዶክስ(መልሱ)… አዎን የክርስቶስ ኢየሱስን ሥራ እዚያ በስፍራቸው ሆነው ያቀጣጥሉ፡፡” ኆኅተ ብርሃን መጋቢት 2002 ገጽ 4

መስቀል፡ የምንቀብረው ወይስ የምንሸከመው?

   ''ከተሰቀለው ከኢየሱስ ጋር እንጂ ከተሰቀለበት መስቀሉ ጋር ምን አለን...'' ለሚሉት ግሩም ምላሽ ይመልከቱ።